ወዴት ወዴት ?
በጭለማ ጉዞ እውር መሪ ሲበዛ፣ ትንሽ የምትመስል ፋኖስ ከትልቁ ብርሃን ጋር አጋናኝታ እ ፍ ፎ ይ ማለታችን እንደማይቀር እርግጠኛ ነን። ኢትዮጵያ እንደዛሬ እጆቿን ወደ ስማይ ዘርግታ የምትጮህበት ጊዜ አልነበረም። „ሀ“ ብለን „ፐ“ ማለታችን አይቀርም[i]።
ውድ አንባቢ ሆይ!
ፋኖሱን ይዘን እንደተከታተላችሁት ቀስ እያልን እየዳበስንና ተጠንቅቀን እየረገጥን „ከጨለማው ዋሻ“ ወደ ብርሃኑ ዓለም ለመውጣት ጥረት እያደረግን ነው።
እንደምናውቀው ውጅንብርና ግርግር ቀውስና መከራ ትርምስና ዝብርቅርቅ ያሉ ነገሮች በአንድ ጊዜ መጥተው በአገራችን ነግሰዋል። እንደዚህ ዓይነቱ ሁኔታ ደግሞ አንድን ሰው ግራ ያጋቡታል። ግራ እሱን የሚያጋቡት ሰው ደግሞ የሚያዘውና የሚጨበጠውን፣ ባለ ባላው ቅርንጫፉም ዛፍ ይጠፋና ለሁሉም ነገር፣ ለሣሩም ለቅጠሉም ለቅራቅንቦውም፣ ሜዳው አመች ሁኖ ያገኘዋል። አውቆም ሆነ ሳይታወቅ ትልቅ ቦታና አተኩሮ ለእነሱም ይሰጣል።
አያድርስ እንጅ ባህር ውስጥ ገብቶ ነፍሱን ለማዳን የሚፍጨረጨር አንድ ሰው እባብ ከአየ መነደፉን ረስቶ እሱን ከመያዝ አይመለስም። …ዘንዶም ወይም አዞም በአጠገቡ ሲላወስ ከአገኘም -አያድርስ ነው- ሕይወቱን ለማደን እነሱንም ለቀም አድርጎ ባህሩ ላይ ቢጋልባቸው ደስ ይለዋል። ቢያንስ ይመኛል። – ቢያንስ ይፈልጋል። እንደዚህ የሚለውን አነጋገርና ምሳሌ አንድ ቦታ ላይ አንስተን ነበር።
አሁን በየአለበት የምንሰማቸውና የምናያቸውም ነገሮች ሁሉ ይህንኑ አነጋገር ያስታውሰናል። ግን ደግሞ እንደ አንዲት ጥርት ያለች „የፓለቲካ ፍልስፍና„ በዚህ የቀውጢ ዘመን ዓይንን የሚትከፍት ጥበብ የለችም።
ወዴት እንደምንሄድ? ምን እነደምንፈልግ? ምን ማድረግ እንዳለብን? ከምን መጠንቀቅና መቆጠብ እንደሚገባን? …በአጭሩ ረጋ ማለትን የምታስተምር ጥሩ ትምህርት ከእሱዋ ሌላ የለም።
ቀደም ሲል ስለሸንጎ አንስተናል።
ከዚያ በፊት ስለ ኢትዮጵያ አንድነት ጽፈናል። ትችት እነደ ሙያ ብለን ስለ ጋዜጣ ሚና በትንሹ ጠቃቅሰን አልፈናል። ….አሁን ደግሞ ስለ ሕግና ስለ የሕግ በላይነት ስለ የሰው ልጆች ሁሉ አንዱ አንዱን ሳይበልጥ እኩል ስለሚጋሩት መብት አንድ አጠር መጠን ያለች “…ስለ ሦስተኛው ምሶሶ“ አንዲት ጽሁፍ አዘጋጅተን እንድትመለከቱት አድርገናል። አውቀን አንድ ቦታ ላይ „ጃንሆይና ነጻ ዜጋ „ የሚለውን አረፍተ ነገር አስገብተናል።
መልሱንም ትችቱንም እዚያው ውስጥ ብቻ ሳይሆን ሁሉም ጽሑፍ ውስጥ ታገኛላችሁ።
ከጨለማ ወደ ብርሃን፣ ከአንድ የዞረበት አስተሳሰብ ወደ ሌላው የቀና አመለካከት፣ ከአንድ የተሳሳተ መንገድ ወደ ቀጥተኛው ቀይሮ ይህቺን ዓለም በሌላ ዓይን መመልከት አስቸጋሪና ከባድ እንደሆነ እናውቃለን።
አውጥተን አውርደን ስናየው ከኢንላይትመንት ፋኖስ፣ ከሚቀጣጠለው ጧፍ ከእሱ ሌላ ምንም መፍትሔ የለም።
በኢንላይትመኔት፣ በጸጋ ልጆች፣ ከእግዚአብሔር በአገኘነው የተፈጥሮ መብታችን (ሌሎቹ ተፈጥሮ ብቻ ይሉታል) ማንም ሰው በዚህች ዓለም ላይ እኩል ሁኖ ስለተፈጠረ፣ ማንም ሰው በሌላው ላይ ተነስቶ የበላይነቱን አሳይቶ „…እኔ ብቻ አውቅልሃለሁ ስለዚህ አንተ አርፈህ ተቀመጥ„ ብሎ መወሰን እንደማይችል እናውቃለን።
ኃይልም፣ ጠበንጃም፣ ጉልበትም፣ እኔ ብቻ የሚባለው ዕብሪትም፣ ሐብትም፣ ገንዘብም የሕዝብ ድጋፍ ከሌለው ውስንና ከንቱ ነው። ሕዝብ ደግሞ የሚፈልገውን ያውቃል።
ምንድነው የሚፈልገው?
ሰው ሥራና ዳቦ፣ ቤትና የግል ሐብት፣ …መሬትና ገንዘብ፣ ፍትህና ፍርድ፣ አለቁጥጥርና ክትትል ነጻ-አየር ተንፍሶ መኖርን፣ ደስታና ፈንጠዚያን፣ ጡረታና እንክብካቤን …አምላኩን አመስግኖ በሰላም ተኝቶ በሰላም መነሳት ነው።
መጻፍና መመራመር የሚፈልጉ አሉ። መምረጥና መመረጥ የሚመኙም አሉ። መተቸት፣ መቃወም….የሚሹም አሉ። ….ይህን የመሰለ ጸጋ፣ የፈለጉትን መናገር፣ የፈለጉትን ማድረግ፣… ለገዢው መደብ ብቻ የተሰጠ ልዩ የአምላክ መብት አይደለም ።
እንደምናውቀው የሰው ልጆች ሁሉ እኩል የሚጋሩት እኩል ከእግዚአብሔር የተሰጣቸው የተፈጥሮ መብታቸው ነው። ይህን መብት ደግሞ አንዱ ከአንዱ አብልጦ ለእራሱና ለዘመዶቹ ብቻ እንዳያደርገው፣ ሁሉም እኩል የሚጋሩት „ሕግ ደንግገው“ የሰለጠኑ ሰዎች አውጥተዋል። እሱም ኢትዮጵያ እራሱዋ የፈረመቺው የዓለም አቀፉ የሰበአዊ መብት አዋጅ ነው።
አሁንም የምናነሳው አርዕስት ተቀድቶ የማያልቀው የነጻ-ዜጋ ጉዳይ ነው። አንድ የሚያደርገን ነገር ቢኖር (እሱ ብቻ አይደለም) የግለሰብ ነጻነት የተፈጥሮ መብታችን ነው።
መልካም ንባብ።
ይልማ ኃይለ ሚካኤል
ዋና አዘጋጅ።
[i] ሀ – እንደ alpha – ሰ – እንደ ሰው ይሆንና – ፐ – እንደ መጨረሻው ፊደላችን ተግልብጦ ና አእምሮ ው ተዘርግቶ ይበስላል፤ ምራቁን ይውጣል!
“The order of the Ge’ez system has remained the same for roughly 3000 years. It is also of note that the determinative sign for the first syllograph Hä, which is “a person standing with both his arms raised towards the heavens” and the corresponding first syllograph, “hoi,” of Ancient Egypt, which is a pictograph of the front end of a lion, are both correlated to “the Ethiopic philosophic evocation of 68 Psalms, Verse 31of the Bible, ‘Ethiopia stretches her hands unto God.”14” (cf. Gabriella F. Scelta)